1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ለንደን ማራቶን፥ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ እና ፈይሳ ሊሌሳ

ቅዳሜ፣ ሚያዝያ 14 2009

ኢትዮጵያውያኑ አትሌቶች ቀነኒሳ በቀለ እና ፈይሳ ሊሌሳ ነገ በለንደን ማራቶን ይፎካከራሉ። የ5,000 እና 10,000 ሜትር የዓለም ክብረ-ወሰኖች ባለቤት የሆነው ቀነኒሳ በቀለ በማራቶን የግል ምርጥ ሰዓቱን ሊያሻሽል ማቀዱን ተናግሯል። ቀነኒሳ በኬንያዊው አትሌት ኤሊውድ ኪፕቾጌ የተያዘውን የውድድሩን ክብረ-ወሰን የማሻሻል ዕቅድ እንዳለውም ገልጧል

https://p.dw.com/p/2bjzG
Kenenisa Bekele und Feyisa Lilesa   Äthiopien  London Marathon
ምስል Reuters/M.Childs Livepic

ኢትዮጵያውያኑ አትሌቶች ቀነኒሳ በቀለ እና ፈይሳ ሊሌሳ ነገ በለንደን ማራቶን ይፎካከራሉ። የ5,000 እና 10,000 ሜትር የዓለም ክብረ-ወሰኖች ባለቤት የሆነው ቀነኒሳ በቀለ በማራቶን የግል ምርጥ ሰዓቱን ሊያሻሽል ማቀዱን ተናግሯል። ቀነኒሳ በኬንያዊው አትሌት ኤሊውድ ኪፕቾጌ የተያዘውን የውድድሩን ክብረ-ወሰን የማሻሻል ዕቅድ እንዳለውም ገልጧል። በሪዮ ኦሎምፒክ ውድድር ባለመሳተፉ ዛሬም ድረስ ንዴት እንደሚሰማው የተናገረው ቀነኒሳ በኦሎምፒክ መድረክ እጆቹን ከፍ አድርጎ በማጣመር የኢትዮጵያ መንግሥትን ተቃውሞ ለስደት የተዳረገው ፈይሳ ሊሌሳን ይገጥማል።

Kenenisa Bekele  Feyisa Lilesa  London Marathon
ምስል Reuters/M.Childs Livepic

የ27 አመቱ ፈይሳ ከሪዮ ኦሎምፒክ በኋላ አስቸጋሪ ጊዜ ማሳለፉን ለፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ተናግሯል። «ለአምስት ወራት ከቤተሰቦቼ ተነጥዬ በአሜሪካ ቆይቻለሁ» ያለው ፈይሳ ዛሬም ድረስ በኢትዮጵያ ሰዎች እየተገደሉ እና ለእስር እየተዳረጉ ነው ሲል ተናግሯል፤ በለንደን ማራቶንም መንግሥትን በመቃወም ምልክት እንደሚያሳይ ገልጧል። ቀነኒሳ እና ፈይሳ በኢትዮጵያ በተለይም በኦሮሚያ ክልል ለተቀሰቀሰው ተቃውሞ እና የመንግሥት ርምጃ ተቃራኒ ምላሾችን ከሰጡ በኋላ ከፍተኛ መነጋገሪያ ሆነው ቆይተዋል። ተስፋዬ አበራ፤ጥላሁን ረጋሳ፤ አሰፋ መንግስቱ በወንዶቹ ጎራ ከቀነኒሳ እና ፈይሳ ጋር ይፎካከራሉ።

ጥሩነሽ ዲባባ፤ አሰለፈች መርጊያ፤ ማሬ ዲባባ፤ አበሩ ከበደ እና ትዕግስት ቱፋ በሴት አትሌቶች ጎራ የሚወዳደሩ ኢትዮጵያውያት ናቸው። የኤርትራ ተወላጆቹ ግራማይ ገብረሥላሴ እና አማኑኤል መሰል እንዲሁም ኬንያውያኑ አቤል ኪሩይ እና ዳንኤል ዋንጂሩም ተፎካካሪዎች ናቸው። በሴቶች ዘርፍ በሪዮ ኦሎምፒክ በ400 ሜትር ከተወዳደረች በኋላ ለስደት የተዳረገችው ሶማሊያዊቷ ዘምዘም መሐመድ ፋራሕ በለንደን ማራቶን ትፎካከራለች።

እሸቴ በቀለ

ማንተጋፍቶት ስለሺ